የቻይና የባለሀብቶች ልዑካን ቡድን የቦሌ ለሚ ልዩ የኢኮኖሚ ዞንን ጎበኘ
ከ30 በላይ የቻይና ባለሀብቶችን ያካተተ የልዑካን ቡድን የቦሌ ለሚ ልዩ የኢኮኖሚ ዞንን ጎብኝቷል።
ልዑካኑን በኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽንና ማርኬቲንግ ዘርፍ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ጃለኔ ሃሰን ተቀብለዋቸዋል።
ወ/ሮ ጃለኔ ለልዑካኑ ኮርፖሬሽኑ በሚያስተዳድራቸው 14 ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖችና ኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚሰጡ አገልግሎቶች፣ የባለሀብቶች የሥራ እንቅስቃሴዎች እና ለኢንቨስተሮች የሚሰጡ ማበረታቻዎች ዙሪያ ገለጻ አድርገዋል።
በግብርና ማሽነሪዎች፣ በኢንዱስትሪ እቃዎች፣ በአግሮ-ፕሮሰሲንግ፣ በታዳሽ ኃይል፣ በሎጂስቲክስ እና በሌሎች ልዩ ልዩ ዘርፎች የተሰማሩ ባለሀብቶችን ያካተተው የልዑካን ቡድን፣ በቀጣይ በኮርፖሬሽኑ በሚተዳደሩ ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖች ውስጥ ኢንቨስትመንት በማካሄድ ሀብታቸውንና እውቀታቸውን በሥራ ላይ እንዲያውሉ ለማስቻል ጉብኝቱ መዘጋጀቱ ተገልጿል።
የልዑካን ቡድኑ ተወካይ ዛው ዚከን (Zhao Zichen) በበኩላቸው፣ ከኮርፖሬሽኑ ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማጠናከር የኢንቨስትመንት ትብብራቸውን ይበልጥ ለማሳደግ፣ የቻይናን ምርጥ ተሞክሮዎች ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት እና ሁለንተናዊ ግንኙነታቸውን ይበልጥ ለማጠናከር ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል።
በጉብኝቱ ማጠቃለያ፣ የልዑካን ቡድኑ አባላት በቦሌ ለሚ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ውስጥ በአልባሳትና ጨርቃ ጨርቅ ዘርፍ የተሰማራውን የሽንትስ ጋርመንት ኩባንያ የምርት እንቅስቃሴውን በቅርብ ተመልክተዋል።