ኮርፖሬሽኑ የ2018 በጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀሙን በሃዋሳ ከተማ መገምገም ጀመረ
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የ2018 በጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀሙን በሃዋሳ ከተማ መገምገም ጀመረ፡፡
የእቅድ አፈፃፀሙን የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሰሃ ይታገሱ፤የማኔጅመንት አባላት፣የሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ አጌና ኔቶ ፣ የኮርፖሬሸኑ መምሪያ ኃላፊዎች እና የልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች ስራ አስኪጆች በተገኙበት ተጀምሯል፡፡
የሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ አጌና ኔቶ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ኮርፖሬሽኑ የሃዋሳ ከተማ ሁለንትናዊ የኢኮኖሚ መነቃቃት እንዲፈጠር ያደረገና አዲስ አቅም የፈጠረ በመሆኑ በአስተዳደራቸው ስም ምስጋናቸውን አቅርበው ይህን አብሮነት አጠናክሮ ለማሰቀጠል ከኮርፖሬሽኑ ጋር ያለው ቅንጅትና ትብብር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሰሃ ይታገሱ (ዶ/ር) በበኩላቸው የ2018 በጀት አመት የእቅድ አፈጻጸም ግምገማ ኮርፖሬሽኑ በቀጣይ 5 ዓመታት የሚመራበት ስትራቴጅ እቅድ ውስጥ የመጀመሪያው አመት በመሆኑ እቅዱን በመገመግም ለቀጣይ በጀት ዓመት ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች አቅጣጫ የሚሰጥበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ኮርፖሬሽኑ በባለፈው በጀት አመት በኮርፖሬሽኑ ታሪክም ሆነ ከባለፈው በጀት ዓመት የተሻለ ውጤት የተመዘገበበትና ለሃገራዊው እድገት የበለጠ አስተዋጽኦ ማበርከት የተቻለበት መሆኑን የገለጹት ዋና ስራ አስፈጻሚው ይህንንም በቀጣይ አመታት አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል፡፡
በግምገማ መድረኩ በበጀት ዓመቱ እንዲሁም በ5 አመት የኮርፖሬሽኑ ስትራቴጅክ እቅድ መሰረት የመጀመሪያ አመቱን አፈጻጸም ለቀጣዩ በጀት ዓመት በሚከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት ላይ አቅጣጫ የሚሰጥበት ይሆናል።